የምርጫው ውጤትን በማስመልከት፣ እንኳን ደስ አላችሁ! (July 10, 2021)

የተከበራችሁ ኢትዮጵያውያን እና ኢትዮጵያውያት

ላለፈው ግማሽ ክፍለ ዘመናት፣ የሀገራችን ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ በነጻ ፈቃዱ የመረጠው መንግሥት እንዲኖረው ብዙ ሙከራዎች ሲደረጉ ቢቆዩም፤ በተለያዩ ምክንያቶች ሲሰናከሉ ነበር። በሂደቱ አያሌ ተማሪዎችና ወጣቶች፣ ገበሬዎችና የቤት እመቤቶች፣ ምሁራንና መለዮ ለባሾች፣ መላው የሀገራችን ሕዝብ ከፍተኛ ዋጋ ከፍሏል። ካለፈ ልምዳችንና ባልተሳኩ ጉዞዎች ጠባሳ ሰበብ፣ የአሁኑም ምርጫ ዴሞክራሲያዊነቱ ተጠብቆ ባይጠናቀቅስ በሚል ስጋት፣ ያለፉትን ወራት እንደ ሀገር በፍርሃት ተወጥረን መክረማችን ሊካድ አይችልም። ኢትጵያውያን ግን ጨዋ ብቻ ሳይሆኑ አርቆ አሳቢ መሆናቸውን ዛሬም አስመስክረዋል። የተሰጋውን ሳይሆን የሚፈልጉትን ማድረግ እንደሚችሉ በግብር አሳይተዋል። ዝናብና ፀሐይ ሳይገድባቸው፣ በረጃጅም ሰልፎች ሳይሰለቹ፣ እስከ እኩለ ሌሊት ታግሰው ፍላጎታቸውን በካርዳቸው ገልጸዋል። እንደ እኛ እምነትም በዚህ ምርጫ አሸናፊ የሆነው ሕዝባችን ነው። ከሕዝባችን በመቀጠል፣ በብዙ ውሱንነቶች ውስጥ አልፈው በዲሞክራሲና በሕዝብ ድምፅ ላይ ባላቸው ጽኑ እምነት፣ ሀሳብና ፖሊሲያቸውን ለሕዝብ አቅርበው ብርቱ ውድድር ያደረጉ ተፎካካሪ ፓርቲዎች የዴሞክራሲያዊ ሂደቱ ድል አድራጊዎች ናቸው።

ይህንን ምርጫ ልዩና ታሪካዊ የሚያደርጉት ብዙ ጉዳዮች አሉ። በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ ከተጽዕኖዎች በተላቀቀ የምርጫ ቦርድ ዳኝነት ያደረግነው ምርጫ መሆኑ አንደኛው ነው። የምርጫ ቦርድ ዳኝነት እንዲሳካ ደግሞ ቁጥራቸው የበዙ የግልና የመንግሥት ሚዲያዎች፣ የሲቪል ተቋማት፣ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ ፍርድ ቤቶችና ሌሎችም ተቋማት በግልጽ የተከታተሉት መሆኑ ሂደቱን ከመቼም ጊዜ በላይ ተአማኒና ዲሞክራሲያዊነቱ የተጠበቀ ምርጫ ያደርገዋል። ምርጫው ዴሞክራሲን የመትከል ግባችንን አንድ እርምጃ ያስኬደ በመሆኑ፣ ፓርቲያችን ከምንም በላይ ቀዳሚ ድሉ አድርጎ ይቆጥረዋል። በታሪካዊው ምርጫ ተሳታፊ መሆን በራሱ የሚፈጥረው ደስታ እንዳለ ሆኖ፣ ፓርቲያችን በሕዝብ ይሁንታ አግኝቶ ሀገር ለማስተዳደር መመረጡ አስደስቶናል። በውጤቱም ከአሸናፊነት ይልቅ ኃላፊነት፣ ከድል አድራጊነት ይልቅ ታላቅ የሆነ ሀገራዊ አደራ እንዲያድርብን አድርጎናል።

መንግሥት የሚመሠረተው በሕዝብ በተመረጡ ፓርቲዎች ቢሆንም ሀገርን መምራትና ማስተዳደር ግን ለተመረጡ ፓርቲዎችና መሪዎች ብቻ የሚተው አይደለም። ተፎካካሪ ፓርቲዎችና መሪዎቻቸውም እስከሚቀጥለው ምርጫ በመንግስት አስተዳድርና ሕዝብን በማገልገል ሂደት ውስጥ ሚናቸው ሰፊ ሊሆን እንደሚገባ ለማስታወስ እወዳለሁ። በቀጣይ ወራት ብልጽግና በሚመሠርተው መንግሥት ውስጥ በአስፈጻሚው አካልም ሆነ በፍርድ ቤቶች፣ በሌሎችም የፌደራልና የክልል ተቋማት ላይ ንቁ ተሳትፎ እንዲኖራቸው፣ በዘንድሮው ምርጫ በኃላፊነትና በብቃት የተወዳደሩ የሕዝብ አለኝቶችን ከዚህ በፊት ካደረግነው በእጅጉ ከፍ ባለና አዎንታዊ ለውጥ በሚፈጥር መልኩ እንደምናካትታቸው ለመግለጽ እወዳለሁ። በተጨማሪም እስከሚቀጥለው ምርጫ የበለጠ ተጠናክረውና ተቋማዊ አቅማቸው ደርጅቶ ብርቱ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ ከማድረግ ወደ ኋላ አንልም። በዚህ ምርጫ የፈጠርነው አሸናፊና ተሸናፊን ሳይሆን፣ ጠያቂና ተጠያቂ ያላበት የዲሞክራሲ ሥርዓትን ነው። በዚህ ደግሞ ያሸነፉት በምርጫው የተሳተፉት ሁሉም አካላት ናቸው።

ውድ የኢትዮጵያ ልጆች፣

በምርጫ ካርዳችሁ ስትመርጡን በዕቅድና በፖሊሲ የያዝናቸውን የብልጽግና ግቦች እንድናሳካ የድፍረትና የጥንካሬ ስንቅ እንደሚያቀብለን ሁሉ፣ እኛና እናንተን ያስተሳሰረው ቃል ኪዳን ተጠብቆ እንዲቆይ ነገሮች አልጋ በአልጋ እንደማይሆኑን እንገነዘባለን። ቢሆንም ግን ከመቼውም ጊዜ በላይ ትከሻችንን አስፍተን፣ ኢትዮጵያን ከሚወዱ አካላት ጋር ሁሉ በትብብር ዐቅማችን አማጥጠን ለመሥራት ቆርጠን እንደተነሣን ሳበስራችሁ ደስ እያለኝ ነው። በቀጣይ ዓመታት ሀገራችን በእውነትም በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ከፍ የምትልበት ዘመን ይሆናል። ይህ እንዲሳካ የሐሳብና የሞራል ስንቅ እንደምታቀብሉን፣ መንገድ ስንስት እንደምትመልሱን፣ ስናጠፋም እንደምታርሙን ተስፋ በማድረግ ነው።

በሀገራችን ሁለንተናዊ ብልጽግና እውን እንዲሆን በቀጣዩ አምስት ዓመት ፈር ጠራጊ እንሆናለን የምንለው፣ በዙሪያችን ባሉና ብልጽግና በሚቀላጠፍባቸው አራት ማዕዘኖች መሐል ቆመን ነው። የመጀመሪያው ማዕዘናችን የመሠረተ ልማት ግንባታ ሲሆን፥ ሀገራችን እንድትበለጽግ በኢኮኖሚውም ሆነ በማኅበራዊና ፖለቲካ ዘርፎች ዘላቂ መሠረት የሚሆኑ፣ በፍጥነት የሚጠናቀቁ፣ ጥራታቸው የተጠበቁ፣ ከብክነት ነጻ የሆኑ እና የምንፈጥራቸውን ተቋማት መሸከም የሚችሉ ትውልድ ተሻጋሪ መሠረተ ልማቶችን መገንባታችንን እንቀጥላለን። ጥቂትም ቢሆኑ ባለፉት 3 ዓመታት አመርቂ ሥራዎችን ለመሥራታችን ምስክሮቹ እናንተው ናችሁ።

ሁለተኛው ማዕዘናችን የተቋማት ግንባታ ሲሆን፣ በጥቂት ግለሰቦችና ነጠላ ተቋማት ላይ ከማተኮር ባለፈ ሀገራችንን በጽኑ መሠረት ላይ የሚያቆሙ ጠንካራ ተቋማት ያስፈልጉናል። ዘመን ተሻጋሪ ሥርዓት ለማጽናት የሚስችሉ ገለልተኛና ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የሚያገለግሉ ተቋማትን መገንባት ላይ ትኩረት ይደረጋል። ይኼ ማሕቀፍ ከፌደራል እስከ ክልል የሚገኙ ተቋማትን የሚያካትት ይሆናል።

በሦስተኛ ደረጃ እንደ ሀገር የሚያስተሳስሩን የጋራ አመለካከቶችና የጋራ ትርክቶች ላይ ትኩረት ሰጥተን ልንሠራባቸው ይገባል። እርስ በእርስ የሚቃረኑና የሚጠፋፉ ትርክቶች ምን ያህል ለጠላቶቻችን ተመችቷቸው እኛን ደካማ እንዳደረገን ያሳለፍናቸው ዓመታት ሕያው ምስክሮች ናቸው። ስለዚህ ክፍተቶቻችንን በሚደፍን መልኩ ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገር አጠንክረው በሚያቆሙን እሴቶች ላይ የተመሰረተ፣ ገዢና ሁላችንንም አሸናፊ የሚያደርግ ትርክት ለመገንባት ጠንክረን እንሠራለን።

በአራተኛ ደረጃ የሞራል ልዕልናና ግብረገባዊነት ተመጣጣኝ ትኩረት አግኝተው እስካልተሠራባቸው ድረስ በሀገራችን ኃላፊነት የሚሰማቸው ዜጎች ቁጥር እየቀነሰ፣ በተቃራኒው ኢ-ሞራላዊ ድርጊቶች እየተስፋፉ እንዲመጡ በር ይከፍታል። ይኼንን ችግር የመቅረፍ ኃላፊነት መንግሥትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ላይ ብቻ የሚጣል ሳይሆን፣ ከግልና ከቤተሰብ ጀምሮ የሚሠራ ሥራ ነው። ሁሉም አካላት ተረባርቦ ሀገርና ትውልዱን እያቆሸሹ ያሉ መጥፎ ተግባሮችን ጠርጎ ሊጥላቸው ይገባል። በቀጣይ ዓመታት በሞራል ንጽህና የተገነቡ ተቋማትንና መሪዎችን አንጥረን የምናወጣበት እንዲሆን ተስፋ አደርጋለሁ።

ውድ የሀገሬ ዜጎች፣

ባለፉት ሦስት ዓመታት በከፍተኛ ጥንቃቄ የቀረጽነው የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለተግባራዊነቱ በጋራ ከተጋን ያለ ጥርጥር ቀጣዩቹ ዓመታት ለሀገራችን ብልጽግና እንደ ወሳኝ የመታጠፊያ ኩርባ ይሆናል። ዕምቅ ዐቅሞቻችን ምንድን ናቸው? ምን ዓይነት የመበልጸግ ዕድል እጃችን ላይ አለ? ምን ብናደርግ ኢኮኖሚያችን መዋቅራዊ ለውጥ ያመጣል? የሚሉትን በሚገባ ፈትሸን ያረቀቅነው ዕቅድ ነው።

በሀገራችን ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ለነገ የማይባል ጉዳይ ነው። በፍጥነት የምግብ ፍላጎታችንን በማሟላት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከውጭ የምግብ ድጎማ መላቀቅ አለብን። ምግብ ለእኛ ቅንጦት መሆን አይገባም። ጠግቦ መብላት ቅንጦት የሆነበት ሕዝባችንን መርጦ መብላት እንዲጀምር ለማድረግ ቆርጠን መነሳት አለብን። በብዝኃ ዕጽዋትና በብዝኃ እንስሳት የምትታወቅ ሀገራችን የእንስሳት ተዋጽዖና ፍራፍሬዎች ለገበታችን ከቅንጦትነት ወደ አዘቦትነት መለወጥ አለባቸው። ዶሮና ዕንቁላል፣ ወተትና ቅቤ፣ ተርፎን ለገበያ የምናቀርባቸው እንጂ ለዓመት በዓል አይተናቸው የሚሰወሩ የሩቅ እንግዳ መሆናቸው ሊያከትም ይገባል።

እዚህ ጋር አንድ መታወቅ ያለበት ሀቅ አለ። መንግስትና ሕዝብ እጅና ጓንት ሆነው እስካልሠሩ ድረስ ሕልማችን ይሳካል ማለት ዘበት ነው። በቀጣይ 5 ዓመታት ተባብረን በተለይ በግብርናው ዘርፍ ምርታማነት ለማሳደግ ጠንክረን መስራት አለብን። ከዚህ ቀደም ጀምረናቸው ውጤት እያመጡ ያሉ ተግባራት አሉ። የበጋ ሰብሎችና ፍራፍሬዎች ላይ ለውጥ ለማምጣት ከተጀመሩ አነስተኛ መስኖዎች ባለፈ፣ ዝናብ አጠርነት ለመዋጋት በቴክኖሎጂ አማካኝነት ደመናን ወደ ዝናብ የመቀየር ልምምዳችን እያደገ ይገኛል። በቅርቡም ምርትን የሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመን ችግሮቻችንን ወደ ዕድል መቀየር ጀምረናል።

አየር ንብረታችንን የሚያስተካክለውና የብዝኃ ዕጽዋትና የብዝኃ እንስሳት ሀብታችንን በእጅጉ ያሳድጋል ተብሎ ተስፋ የተጣለበት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብራችን እንዲሁ ተጠቃሽ ነው። በቁጥር ግንባር ቀደም ያደረጉን የቀንድ ከብቶቻችን ከመቀንጨር ወጥተው ምርታማ እንዲሆኑ ያደርጋል። ወደየጎረቤት ሀገሩ የሸሹ የዱር አራዊትም ተመልሰው፣ ከታሪካዊና ባህላዊ መስህቦች ጋር የተዋደደ ተፈጥሮአዊ መስህብ በመሆን የቱሪስት ፍስትን እንዲጨምርና ኢኮኖሚያችን መስፈንጠር እንዲችል መደላድል ይሆናል ብዬ አምናለሁ።

የሀገራችን ሕዝብ ሆይ፤

ባለፉት ጥቂት ዓመታት ትኩረታችንን ሰቅዘው ከያዙት ጉዳዮች መካከል ሌላኛው የሕዳሴ ግድብን የተመለከተ ጉዳይ ነው። የዴሞክራሲ ጥያቄን አንድ ምዕራፍ ለማሳደግ የምርጫችን መሳካት ወሳኝ እንደነበረው ሁሉ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ችግራችንን ለመቅረፍና ለዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች መቀላጠፍ ጉልህ አስተዋጽዖ ከሚያበረክቱ ፕሮጀክቶቻችን መካከል አንዱና ወሳኙ የሕዳሴ ግድብ ግንባታችን እንደሆነ ይታወቃል።

የሕዳሴ ግድብ አጀንዳ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ከግድብም፣ ከኤሌክትሪክ ኃይል ምንጭነትም በላይ ነው። ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ባለፈ ዳግም የመነሣታችን ተምሳሌት ነው። በራስ ዐቅም የመቆም፣ በራስ ፍላጎት የመመራት፣ የሉዓላዊነታችን ምልክት፤ የሀገራዊ አንድነታችን ገመድ ነው። በሕዳሴ ጉዳይ ብዙ አይተናል፣ ብዙ ተፈትነንበታል። በራሳችን ዐቅም መቆማችን የሚያስደነግጣቸው፣ በፍላጎታችን መመራት መጀመራችን የሚቆጫቸው ብዙ ጋሬጣዎችን ሲጥሉብን ነበር። “ሚስማር አናቱን ሲመቱት ይበልጥ ይጠብቃል” እንዲሉ ሆኖ፤ በዓባይ ጉዳይ በገፉን ቁጥር እየቆምን፣ በተጫኑን ቁጥር እየበረታን፣ ባዋከቡን ቁጥር ይበልጥ እየጸናን አሁን የደረስንበት ቦታ ላይ ቆመናል። በቅርቡ ሁለተኛውን ዙር የውኃ ሙሌት አድርገን፣ በምርጫው ስኬት የተደሰትነውን ያህል፣ በሕዳሴያችንም ሐሴት እንደምናደርግ አልጠራጠርም።

በሕዳሴ ግድብ ላይ ፍትሐዊ ተጠቃሚነታችን እንዲጠበቅልን እንጂ መቼም ቢሆን ሌሎች ሀገራትን የመጉዳት ፍላጎት ኖሮን አያውቅም። አሁንም ለታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ደግመን ማረጋገጥ የምንፈልገው ሐቅ፣ የዓባይ ወንዝ እንደሚያስተሳስራቸው ወንድም ሕዝቦች በእናንተ ላይ ምንም ዓይነት አሉታዊ ተጽዕኖ የመፍጠር ፍላጎት የለንም። ዛሬም ሆነ ወደፊት በጋራ ተጠቃሚነት ዙሪያ ለመመካከር በራችን ክፍት ነው። እኛንም ሆነ እናንተን ነጥሎ ተጎጂ ወይም ተጠቃሚ በሚያደርጉ አካሄዶች ላይ እንድንሳተፍ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን አይፈቅም።

ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያለንም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከዚህ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን የሚቀዳ ነው። በጋራ ተጠቃሚነት ዙሪያ ለመሥራት ሁሌም ዝግጁዎች ነን። የአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ሰላሙ እንዲጠበቅ፣ የጋራ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ማኅበረሰብ እንዲፈጠር፣ በትብብርና በመግባባት እንድናድግ ኢትዮጵያ ትፈልጋለች፤ ጥሪም ታቀርባለች።

የተከበራችሁ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፣

የሀገራችን መጻኢ ጊዜ ብሩህ ለማድረግ በተገቢው መወጣት ከሚገቡን የቤት ሥራዎች መካከል አንዱና ዋነኛው ፖለቲካዊ ጉዳዮቻችንን በሠለጠነ መንገድ መምራት ነው። ከላይ በመግቢያዬ እንደገለጽኩት ይኼ ኃላፊነት በመንግሥትና በተመረጠው ፓርቲ ላይ ብቻ የሚጣል አይደለም፤ አንድ አካል ልሥራው ብሎ ቢነሣ እንኳን በአግባቡ የሚወጣው ጉዳይ እንዳልሆነ በተደጋጋሚ አይተናል። እንኳንስ የሠለጠነ የፖለቲካ ሥርዓት መገንባትን የሚያህል ነገር ይቅርና፣ አንድ ዙር ምርጫን ዴሞክራሲያዊ አድርጎ ለማጠነቀቅ ብዙ አካላት መረባረብ እንዳለባቸው ካለፍናቸው ምርጫዎች በሚገባ ተረድተናል። የዘንድሮውንም ምርጫ ካለ እናንተ ድጋፍና ትብብር ፍትሐዊና ዴሞራሲያዊ በሆነ መንገድ ማከናወን ባልተቻለ ነበር።

በቀጣይም ዓመታት የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ሂደታችን መሬት እንዲረግጥ የተለመደ ትብብራችሁና በየምዕራፉ ያላሰለሰ ድጋፋችሁ እንደሚያሻን ከወዲሁ ለመግለጽ እወዳለሁ። በሀገራችን የብልጽግና ጉዞ ውስጥ የሚኖራችሁ ድርሻ ወሳኝ እንደሆነ እናምናለን።

የፖለቲካ ልዩነቶቻችን እንዳሉ ሆነው፣ ለሀገርና ለሕዝባችን በሚጠቅሙ ማናቸውም የፖለቲካና ኢኮኖሚያዊ አጀንዳዎች ላይ ከእናንተ ጋር በመግባባት ለመሥራት ዝግጁዎች ነን።

ምርጫውን ስኬታማ ያደረጋችሁ ውድ የተቋማት አመራሮችና ሠራተኞች፣

ይህ ምርጫ የተሳካ እንዲሆን የምርጫ ቦርድ አመራሮችና ሠራተኞች፣ እንዲሁም የምርጫ አስፈጻሚዎችና ታዛቢዎች ሁሉ ከደም መሥዋዕትነት በመለስ ያለ ከፍተኛ ዋጋ ከፍላችኋል። ከግራ ከቀኝ የሚመጡትን ጫናዎች ተቋቁማችሁ በውጣ ውረዶች ሳትበገሩ ለሀገራችን የማይደበዝዝ የዴሞክራሲ አሻራ አትማችኋል፤ በዚህም ታሪክ ስማችሁን አድምቆ ይጽፈዋል።

የጸጥታ አካላት፤ ምርጫው ሰላማዊ እንደሆን ጉልህ ሚና ተጫውታችኋል፤ እናንተ ዕንቅልፍ አጥታችሁ ሥጋቶቻችን ሁሉ እንደ ጉም እንዲተንኑ ስላደረጋችሁ ክብር ይገባችኋል። በተመሳሳይ፣ ፈጣንና ሚዛናዊ መረጃን ወደ ሕዝቡ በማድረስ በኩል የግልና የመንግስት ሚዲያዎች፤ እንዲሁም አጭር የጽሑፍ መልዕልት ስርጭት በኩል የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ሠራተኞች፣ ላበረከታችሁት አስተዋጽዖ ኢትዮጵያ ታመሰግናችኋለች።

ውድ የፓርቲያችን አመራሮችና አባላት፣

በዚህ ምርጫ ሕዝቡ ያስተላለፈውን መልእክት በሚገባ መረዳት የወደፊቱን መንገዳችንን ቀና እንደሚያደርገው እናምናለን። ሕዝቡ በአብላጫ ድምጽ እኛን የመረጠው ፓርቲያችን እንከኖች ስለሌሉበት አይደለም፤ ከነስሕቶቻችንን ዕድል ሰጠን እንጂ ድል አላደረግንም። ሕዝብ የመረጠን በአንድ በኩል ያጠፋናቸውን እንድናርም፣ በሌላ በኩል መልካም ጅማሮዎቻችንን እንድናስቀጥል፣ ከሀገር ግንባታ አንጻር በወሳኝ ደረጃ ላይ ያሉ የለውጥ ሥራዎችን በቀጣይ ጊዜያት ፈጽመን እንድናሰረክብ ነው። ሕዝባችን ጉድለቶቻችንን በሚገባ ያውቃል። ከስርቆት ዓመል ያልተላቀቁ፣ ለሰው ነፍስ ግድ የሌላቸው፣ ሕግን የማያከብሩ፣ ኃላፊነታቸውን የማይወጡ አመራሮች በመካከላችን መኖራቸውን ጠንቅቆ ያውቃል። ድምፁን ሲሰጠን ታረሙ፣ ውስጣችሁን አጥሩ እያለን ጭምር ነው። እኛም በተግባር ሆነን ማሳየት አለብን። ይኼን ማድረግ ካልቻልን ከአምስት ዓመት በኋላ በካርዱ እንደሚቀጣን እናውቃለን።

በአሁኑ ምርጫ መምረጥ ያልቻላሁ ወገኖቻችን በሙሉ፣

በልዩ ልዩ የጸጥታና የደኅንነት ምክንያቶች፣ እንዲሁም በሎጅስቲክና በተለያዩ ውሱንነቶች ምርጫው በተያዘለት ክፍለ ጊዜ መሠረት ከተቀረው ሕዝብ ጋር አብራቸሁ ድምፅ ባለመስጠታችሁ ታላቅ የሆነ ቅሬታ ፈጥሮብናል። ይኼ የሆነው ባልተጠበቁ ምክንያቶች እንደሆነ ግንዛቤ ትወስዳላችሁ የሚል ግምት አለን። ሁኔታዎች ተስተካክለው የምርጫ ቦርድ በወሰነው ቀን ምርጫው እንደሚደረግ እምነቴ ነው።

ትግራይን በተመለከተ የትግራይ ሕዝብ በሚፈልገው መንገድ ከተደራራቢ ችግር የሚወጣበትን፣ ተያያዥ ሀገራዊ ችግሮች የሚፈቱበትን እና ሰላምና ደኅንነት የሚረጋገጥበትን የመፍትሔ አቅጣጫ እንከተላለን።

በመጨረሻም፣ ከለውጡ ጊዜ አንሥቶ እስከ ዛሬ ድረስ ስለ ሀገር አንድነትና ስለ ሕዝባችን ተጠቃሚነት ቀና ቀናውን በማሰብ በመንገዳችን ሁሉ ድጋፍ ሲያደርጉልን የነበሩ አካላትን ከልብ ሳላመሰግን አላልፍም። ኢትዮጵያ በታሪክ ለውጥ ላይ ናት። በዚህ የለውጥ ሂደት ተሳፍረን የተሻለች ሀገር እንገነባለን። በዚህ ምርጫ ኢትዮጵያችን አሸናፊ ስለሆነች በድጋሚ ለመግለጽ እወዳለሁ። ቀጣይ ዘመናችንን ብሩህ ያድርግልን፤ ሁላችንም እንኳን ደስ አለን።

ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!

ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ!

ሀምሌ፣ 2013 ዓ.ም

No photo description available.
No photo description available.
No photo description available.
No photo description available.
0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *